Background
Daily Devotional
የዕለቱ ጥቅስ

ነሐሴ

15

ይመለከተዋል

የዕለቱ የመጽሐፍ ቅዱስ ንባብ ክፍል -

መዝ 138፡ 4-6

ይመለከተዋል

“እግዚአብሔር በከፍታ ስፍራ ቢሆንም፣ ዝቅ ያለውን ይመለከተዋል፤ ትዕቢተኛውን ከሩቅ ያውቀዋል።” መዝ 138፡ 6


በሃብት ወይም በስልጣን አድገው “ከተራነት” ወደ “ኀያልነት” ከፍ ሲሉ ዝቅ ባለው ስፍራ አብረዋቸው የነበሩትን የሚያስቡ ስንቶች ይሆኑ? በአብዛኛው የሚታየው ግን ከፍ ባልን ቁጥር ዝቅ ያሉትን ስንረሳ፣ ስንንቅ አልፎም ጉልበታችንን አላግባብ በመጠቀም ስንረግጥ ነው። በእግዚአብሔር ዘንድ የምናየው ግን የዚህን ፍጹም ተቃራኒ ነው።  አምላካችን እግዚአብሔር የኀያላን ሁሉ ኀያል፣ ዙፋኑም ከዙፋናት ሁሉ በላይ ነው። ንጉስ ሰለሞን የዚህን አምላክ ታላቅነት ሲገልጽ እንዲህ ነበር ያለው:-  “እነሆ፤ ሰማይ፣ ከሰማያትም በላይ ያለው ሰማይ እንኳ ይይዝህ ዘንድ አይችልም፤” (1 ነገ 8:27) ምንም እንኳን እርሱ እንዲህ ከአእምሮችን በላይ ታላቅ የሆነ አምላክ ቢሆንም ዝቅ ያለውን ይመለከተዋል፤ ማንንም አይንቅም። 

“ውሆችን በዕፍኙ የሰፈረ፣ ሰማያትን በስንዝሩ የለካ፣ የምድርን ዐፈር በመስፈሪያ ሰብስቦ የያዘ፣ ተራሮችን በሚዛን፣ ኰረብቶችንም በመድሎት የመዘነ” ይሄ ታላቅ አምላክ ከእርሱ ግዙፍነት ጋር ስንነጻጸር ፈጽሞ ኢምንት የሆነውን እኛን ለመፈለግ ዝቅ አለ። ከዙፋኑ ወርዶ በእኛ ሥጋ ውስጥ አደረ። በመካከላችን ተመላለሰ። ይህም በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ምድር መምጣት ተፈጸመ። ከዙፋኑ ወርዶ፣ የሰውን ተፈጥሮ ወስዶ ወደ ምድር መምጣቱ ሳያንስ በክብር ስፍራ በቤተመንግስት ሳይሆን በበረት ተወለደ። በምቾት ተንደላቆ ማደግ ሲችል፣ መልካም አይወጣባትም በተባለች በናዝሬት ከተማ፣ በአናጺነት ሙያ ተሰማርቶ አደገ። የመጣበትንም ተልእኮ ለመፈጸም ወደ አደባባይ ሲወጣ ውሎው ከተናቁትና ከተጠሉት በሰው ዘንድ ስፍራ ከማይሰጣቸው ጋር ነበር። በመጨረሻም በሁለት ወንበዴዎች መካከል በመስቀል ላይ የሁላችንን ሃጢአት ተሸክሞ ህይወቱን ሰጠ። ይህን ሁሉ ያደረገው ደግሞ በሃጢአት ውስጥ የወደቀውን ሰብአዊ ዘር ለመታደግ ነበር።

የሚያሳዝነው እውነታ ታዲያ እንዲህ ዝቅ ብሎ ሊፈልገን የመጣውን ጌታ ሊቀበሉት ያልወደዱ መኖራቸው ሲሆን እነርሱም በትእቢት ልባቸው ተወጥሮ የነበሩ ራሳቸውን ጻድቅ አድርገው የሚያዩ ሰዎች ነበሩ። በእርግጥም መዝሙረኛው እንዳለው “እግዚአብሔር በከፍታ ስፍራ ቢሆንም፣ ዝቅ ያለውን ይመለከተዋል፤ ትዕቢተኛውን ከሩቅ ያውቀዋል።” እኛስ ይህ ከፍ ያለ ታላቅ አምላክ ዝቅ ብሎ እጆቹን ሲዘረጋልን በትህትና ወደ እርሱ የምንቀርብ ነን ወይስ በትእቢት ጥሪውን የምንገፋ?

አባት ሆይ፣ አንተ ታላቅ ሆነህ ሳለ እኛን ለመፈልግ ዝቅ ብለህ የምትቀርበን መልካም አምላክ መሆንህን በማስተዋል እኛም በትህትና ካንተ ጋር መራመድ እንድንችል በጸጋህ እርዳን። አሜን።

Devotion Image
መስከረም
ጥቅምት
ህዳር
ታህሳስ
ጥር
የካቲት
መጋቢት
ሚያዚያ
ግንቦት
ሰኔ
ሐምሌ
ነሐሴ